በዋቤ መስጊድ ማን ቦንብ አፈነዳ? ለምን?
ባለፈው ዓርብ በመላው አገሪቱ አንድ ወጥ የ”ድምጻችን ይሰማ” የተቃውሞ ድምጽ ለማሰማት የወጣውን መርሃ ግብር ተከትሎ የፌደራል ፖሊስ እስከ ግድያ ሊደርስ የሚችል ርምጃ ለመውሰድ እንደሚገደድ የሚያመላክት መግለጫ አውጥቶ ነበር። የድምጻችን ይሰማ አመራር መሆናቸውን የሚገልጹት ክፍሎች ፌደራል ፖሊስ ያወጣውን መግለጫ ተከትሎ ተቃውሞው እንዲቀር መመሪያ ማስተላለፋቸውን ይናገራሉ። በዋቤ መስጊድ ቦንብ ያፈነዳው ማን ነው? ለምን እንዲፈነዳ ተደረገ?
ፖሊስ በከረሩ ቃላቶችና በማስጠንቀቂያ አጅቦ ባወጣው መግለጫ ” … አክራሪ ወሃቢ ሰለፊዎች ላይ ተገቢውን ክትትል በማድረጉ ፖሊስ ለሚወስደው ርምጃ ተገቢውንና የተለመደውን ትብብር እንዲያደርግ ጥሪያችንን በድጋሚ እናቀርባለን” በማለት አስፈራርቶ ነበር። “ምንደኛ፣ ከውጪ በሚላክላቸው ንዋይ ዓይናቸው ታውሮ አርብ በመጣ ቁጥር በተመረጡ መስጊዶች ሁከትና ብጥብጥ ለመፍጠር ጥረት የሚያደርጉ …” በማለት በመግለጫው አስቀድሞ እንደፎከከረው በኮፈሌ ብቻ ከፍተኛ ሰብዓዊና ቁሳዊ ጥፋት መድረሱ ተረጋግጧል።
አስፈላጊውን ድርጊት መርሃ ግብርና የተቃውሞ ደንብ በማስተዋወቅ ከአዲስ አበባ ለአሜሪካ ሬዲዮ መግለጫ የሰጡት አስተባባሪ ኮሚቴ እንዳሉት አቶ መለስ በህይወት እያሉ በ1997 ተቃዋሚዎች ላይ ርምጃ እንዲወሰድ ከሰጡት ትዕዛዝ ጋር ተመሳሳይነት ያለው መግለጫ በመተላለፉ ተቃውሞው እንዲቀር ተደርጓል።
ሰላማዊ የተባለውን ተቃውሞ ከማከናወን ቢቆጠቡም ከአርብ የጁምአ ስግድት አስቀድሞ በየቤቱ በመዘዋወርና በሰላማዊ መንገድ የአምልኮ ስርአታቸውን ለመፈጸም ወደ ተለያዩ መስጊዶች ካቀኑ ምዕመናን መካከል ቀላል ቁጥር የሌላቸው ታስረዋል። ለቪኦኤ መግለጫ የሰጡት የድምጻችን ይሰማ ተወካይ ካንድ ሺህ በላይ ሰዎች መታሰራቸውን አመልክተዋል።
ከመንግስትና የድምጻችን ይሰማ አስተባባሪ ነን ከሚሉት አካላት የሚወጡትን መረጃዎች ሁለት ጽንፍ የያዙ በመሆናቸው በማጣራትና አግባብነት ያለው ትክክለኛ መረጃ ለመስጠት የዝግጅት ክፍላችን ተቸግሯል። በዚህም የተነሳ የተሟላ መረጃ ለማግኘት ያደረግነው ጥረት እንዳለ ሆኖ ባብዛኛው ዘገባችን ከማህበራዊ ገጽ በሚገኙ ዜናዎችና ከመንግስት ድረገጾች እንዲሁም ከአሜሪካ ሬዲዮ ባገኘነው መረጃ የተወሰነ ሆኗል።