Wednesday, 3 April 2013

ጄኔቫ ስደተኞች በየመን

ከየመን መውጣት የተሳናቸው ስደተኞች ቁጥርና የሚገኙበት ሁኔታም እጅግ አሳሳቢ መሆኑን ዓለም ዓቀፉ የስደት ጉዳዮች  ድርጅት በእንግሊዘኛው ምህፃር IOM አስታወቀ ። የድርጅቱ ቃል አቀባይ ጁምቤ ኦማሬ ጁምቤ ከጄኔቫ ስዊትዘርላንድ በሰጡት መግለጫ በጎርጎሮሳውያኑ 2010 ፣ 53 ሺህ የነበረው የመን የሚገኙ ስደተኞች ቁጥር ባለፈው አመት ከእጥፍ በላይ አድጎ 107 ሺህ ደርሷል ። ከነዚህም አብዛኛዎቹ ኢትዮጵያውያን ሲሆኑ የሶማሊያና የኤርትራ ስደተኞችም ያመዝናሉ ። በተለይ ስደተኞቹ ወደ ሳውዲ አረቢያ ለመሻገር የሚመርጧት ሃራድ የተባለችው ከተማ በሺህዎች የሚቆጠሩ ስደተኞች መነኻሪያ  ናት ። ገንዘብ የሌላቸውና መድሐኒትም የማያገኙት እነዚሁ ስደተኞች የሚያድሩት አውላላ ሜዳ ላይ መሆኑን  ቃል አቀባዩ ተናግረዋል ። ከዚህ ሌላ በሰሜናዊው የሃራድ ከተማ የሚገኝ ሆስፒታል ማንነታቸው ባልታወቀ ስደተኞች አስከሬኖች  የተሞላ መሆኑንንም አስታውቀዋል ። በህገ ወጥ መንገድ ሰዎችን ከአገር ወደ አገር ከሚያሻግሩ ሰዎችና ፣  ከአፋኞች አምልጠው ወደ ድርጅቱ ቢሮዎች የሚመጡ በራካታ ስደተኞች አካላቶቻቸው ጉዳት የደረሰባቸው እንደሆኑም ቃል አቀባዩ ተናግረዋል ። ድርጅቱ ባጋጠመው የገንዘብ ችግር ምክንያት ሃዳር ውስጥ ለ 3ሺህ ስደተኞች ያቀርብ የነበረውን ምግብ አቅርቦት   3 መቶ ለሚሆኑ ሴቶች አዛውንትና ብቻቸውን ለሚኖሩ ወጣቶች ብቻ ነው የሚሰጠው  ። በገንዘብ እጥረት ምክንያት ድርጅቱ ያካሂድ የነበረው በፈቃድ ወደ ሃገር የመመለስ መርሃ ግብርም ለማቋረጥ መገደዱን ቃል አቀባዩ አስታውቀዋል ።

No comments:

Post a Comment